ፍኖተ ዴሞክራሲ የኢትዮጵያ አንድነት ድምፅ
በኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) እየተዘጋጀ የሚቀርበው የፍኖተ ዴሞክራሲ የኢትዮጵያ አንደነት ድምጽ ራዲዮ
የፕሮግራም ስርጭቱን በቀጥታ ወደ ኢትዮጵያና የአካባቢ አገሮች ከመጋቢት 23 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሯል።
ይኸው ፕሮግራም በቀጥታም በኢንተርኔት አማካይነት በመላው ዓለም ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያንም እየተዳረሰ ነው።
ፍኖተ ዴሞክራሲ ለመጀመሪያ ጊዜ ስርጭቱን ማስተላለፍ የጀመረው በ1982 ዓ.ም. የኢሕአፓ ሠራዊት ኢሕአሠ በወቅቱ ነጻ
ካወጣው አካባቢ ነበር። ለተወሰነ ጊዜ አጥጋቢ በሆነ ሁኔታ ሥርጭቱን ካስተላለፈ በኋላ ሰራዊቱ በወያኔ፡ በሻዕቢያና በሱዳን
ትብብር ከፍተኛ ጥቃት ስለደረሰበት ሊቋረጥ ችሏል።
በ1992 ዓ.ም. ሥርጭቱን እንደገና ጀምሮ እስከቅርብ ጊዜ ድረስ በአጭር ሞገድ በሳምንት ሁለት ጊዜ በአንድ ወቅትም
በሳምንት ሶስት ጊዜ የተለያዩ ፕሮግራሞችን ሲያስተላልፍ መቆየቱ ይታወሳል። የራዲዮ ጣቢያው በፕሮግራሞቹ ስፋትና ጥልቀት እንዲሁም
በሚያቀርባቸው መረጃዎች ተዓማኒነት የአድማጮችን ድጋፍና ተወዳጅነት እንዳገኘ ለፍኖተ ዴሞክራሲ ራዲዮ ሲላኩ ከነበሩ ደብዳቤዎች
ማረጋገጥ ይችላል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሥልጣን ላይ ያለው የወያኔ ቡድን ባደረገው ተከታታይና ጠንካራ የሞገድ አፈና በአጭር ሞገድ
የነበረው የፕሮግራም ስርጭት እንዲቋረጥ ተደርጎ በሳተላይት አማካይነት ማሰራጨት ጀምሯል።
የፍኖተ ዴሞክራሲ የኢትዮጵያ አንድነት ድምፅ ዓላማ አንድ ነው። የሕዝብን የማወቅ መብት ተግባራዊ ማድረግ-። የሕዝብ የማወቅ
መብትና ሌሎችም ዴሞክራሲያዊና ሰብአዊ መብቶቹ የማይሻሩ የማይገረሰሱ ናቸው። በሥልጣን ላይ ያለው የወያኔ ቡድን ኃይሉንና
ሥልጣኑን መከታ አድርጎ እነዚህን መሠረታዊ የሕዝብ መብቶች ለማፈን ቢሞክርም በትግል ተግባራዊ ይሆናሉ።
መጋቢት 23 ቀን 2007 ዓ.ም. የጀመረው የፍኖተ ዴሞክራሲ የሳተላይት ስርጭትም የዚሁ ትግል አንዱ አካል ነው። ባለፉት
ዓመታት ፍኖተ ዴሞክራሲ የሕዝብን የማወቅ መብት ተግባራዊ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት ያደረገ ከመሆኑ በላይ የሕዝብን መብት ያፈነው
አስከፊው አገዛዝ ተወግዶ በእኩልነት ላይ የተመሰረተ አንድነትን፣ ነጻነትን፣ የመብት መረጋገጥን እና የሕግ የበላይነትን
የሚያስተናግደው ዴሞክራሲዊ ስርዓት እውን እንዲሆን ሕዝቡ እያደረገ ላለው ትግል አስተዋጾ አድርጓል።
ፍኖተ ዴሞክራሲ የኢትዮጵያ አንድነት ድምጽ ተዓማነት ያላቸው ዜናዎችን፤ የዜና ዘገባዎችን፤ በዋና ዋና የአገራችን የፖሊቲካ
የኢኮኖሚና የሶሻል ጉዳዮች ላይ የሚቀርቡ ጥናታዊ ትንታኔዎችና ትችቶችን፤ አቅጣጫ ጠቋሚ ሀተታዎችን ወዘተ…. ለሕዝብ ሲያቀርብ
ቆይቷል። በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ስለጉዳዩ ግንዛቤና ተመክሮ ያላቸውን ዜጎች በቃለ ምልልስ ሀሳባቸውን ለሕዝብ እንዲያካፍሉ
አድርጓል፤ ከአድማጮቹም የሚላኩለትን ደብዳቤዎች በማሰማት ለሕዝብ መረጃውና አስተያየቱ መልሶ ለሕዝብ እንዲዳረስ አድርጓል።
ከዛሬ ጀምሮ በየቀኑ ለሁለት ሰዓት ያህል ለማስተላለፍ ባቀደው ፕሮግራም እነዚህንና ሌሎች ተጨማሪ ፕሮግራሞችን አጠናክሮ
በማቅረብ የአድማጮችን ፍላጎት ለማርካት ከፍተኛ ጥረት የሚያድረግ መሆኑን እንገልጻለን። የሁሉም ሀገር ወዳድ ዜጋ ትብብር
እንደማይለየንም እናምናለን።
መጋቢት 23 ቀን 2007 ዓ.ም.
|